Monday, January 27, 2014

ሰው ይናፍቀኛል

አገሩን የሚወድ በእውነተኛ ፍቅር
ነገን የሚመለከት በትናንት የማይኖር
ሰውን በሰውነት ዘወትር የሚያከብር
ሰው ይናፍቀኛል ለሰው ልጅ የሚኖር
ክፋት ምቀኝነት ተንኮል የሌለበት
ልቡ በጥላቻ ያልተሸነፈበት
በዘመን መካከል የማይለዋወጥ
የኋላውን ረስቶ ወደ ፊት የሚሮጥ
ሁሌ ሰው ያምረኛል ፍቅር የሚሰጠኝ
በደካማ ጎኔ ቆሞ የሚረዳኝ
ሳጠፋ የሚመክረኝ በቅንነት መንፈስ
ድካሜን የሚሸከም ብርታቴን የሚያወድስ
ሰው ይናፍቀኛል ሰውን የሚያፈቅር
ወደ ፊት እያየ በትናንት የማይኖር
በትዕግስት እንድሮጥ አቅም የሚሆነኝ
ችግሬን ተጋርቶ ደስታ የሚሰጠኝ
ህልሜን የሚፈታ ምኞቴን የሚካፈል
ጉልበቴ ሲደክም ሸክሜን የሚያቃልል
በፍቅር እየኖረ ፍቅር የሚያስተምረኝ
ሰው ይናፍቀኛል ሁሌ የሚኖር አብሮኝ
አማራ ነህ ትግሬ ወይስ ነህ ኦሮሞ
እያለ የማይጮህ ከምባታና ጋሞ
ነፍሴን የማያዝል በነገር ቡትቶ
ሰው ይናፍቀኛል ሰው የሚሆን ሰርቶ
በጥላቻ የማይኖር ፍቅር የበዛለት
ለአገር ለወገኑ የሚኖር በቅንነት
በአዲስ አስተሳሰብ ነፍሱ የተሞላ
በዘረኝነት መርዝ ጉልበቱ ያልላላ
ሁሌ የሚመለከት በፍቅር መነፅር
ያለውን አካፍሎ ለወገኑ የሚኖር
ሰው ይናፍቀኛል ነገን የሚያሳየኝ
በኢትዮጵያዊነት ልቤን የሚገዛኝ።

ጥር 19 ቀን 2006 ዓ•ም
አዲስ አበባ
ኢትዮጵያ
የኢትዮጵያ ትንሳኤ በቅርብ እውን ይሆናል!!!

No comments:

Post a Comment